የፈረንሳይ ፕሬዚዳንት ኢማኑኤል ማክሮን በኬንያ ናይሮቢ በተካሄደው የአፍሪካ ፎርዋርድ ጉባኤ ላይ ለአፍሪካ ሀገራት 23 ቢሊየን ዩሮ ኢንቨስትመንት ጥቅል አስታወቁ።
ጉባኤው በፈረንሳይ ፕሬዚዳንት ኢማኑኤል ማክሮን እና በኬንያ ፕሬዚዳንት ዊሊያም ሩቶ በጋራ የተዘጋጀ ሲሆን ከ30 በላይ የአፍሪካ ሀገራት መሪዎችን አሰባስቧል። ውይይቶቹ በአረንጓዴ ኢንዱስትሪ፣ የኢነርጂ ሽግግር፣ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ፣ ዲጂታል ቴክኖሎጂ እና ዘላቂ ግብርና ላይ ተደርገዋል።
የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የአገራቸውን ተሞክሮ በአረንጓዴ ኢንዱስትሪ ልማትና የኃይል ሽግግር ላይ አካፍለዋል። ኢትዮጵያ በእነዚህ ዘርፎች የጀመረችውን ሥራ በማጠናከር የላቀ ሚና እንደምትቀጥል አረጋግጠዋል።
ፕሬዚዳንት ማክሮን የኢንቨስትመንት ጥቅሉ በኢነርጂ፣ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ፣ ባህርና ሎጂስቲክስ እንዲሁም በግብርና ዘርፎች ተግባራዊ እንደሚሆን ተናግረዋል። ይህ ጥቅል 250 ሺህ ቀጥተኛ የስራ እድሎችን ይፈጥራል ተብሏል። ጉባኤው ከፈረንሳይኛ ተናጋሪ ሀገራት ውጭ ለመጀመሪያ ጊዜ የተካሄደ መሆኑን ሮይተርስ እና ፍራንስ 24 ዘግበዋል።