ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የጋራ ሥራችን ኢትዮጵያ ያላትን ሀብቶች መግለጥ፣ ማሳደግ እና መጠበቅ ለቀጣዩ ትውልድ መሠረት መጣል እንደሆነ ተናግረዋል። በባሌ ዞን በተካሄደው ጉብኝት የፊንጫ ሀበራ ፏፏቴን ተመልክተዋል።
አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 9፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከተለያዩ አመራሮች ጋር በባሌ ዞን በተካሄደው ጉብኝት የመጨረሻ መዳረሻቸው የሆነው አስደማሚ የፊንጫ ሀበራ ፏፏቴ ነበር።
በማኅበራዊ የትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት እንዳሉት፥ ባለፉት ሶስት ቀናት በጉብኝቱ የተሳተፉ የቀድሞ አመራሮች እና በሥራ ላይ ያሉ ኃላፊዎች የተፈጥሮ፣ የባሕል እና የሰው ኃብት ከፍ ያሉ መነሳሳትን ፈጥረዋል። “ኢትዮጵያ ለሁሉም የሚበቃ ሀብት እንዳላት እናውቃለን፥ የጋራ ሥራችን እኚህን ሀብቶች መግለጥ፣ ማሳደግ፣ በሀብቶቹ ላይ በመጨመር ቀጣዩ ትውልድ ችቦውን ተረክቦ እንዲቀጥል መሠረት መጣል ነው።” ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትሩ።
ይህ ፏፏቴ በግርማ የሚወርደው ወደ ሶፍኡመር የዋሻ ሥርዓት የሚደመረውን የወይብ ወንዝ የሚቀላቀል መሆኑን ጠቅሰው፥ አካባቢው የኢትዮጵያ ቀይ ቀበሮ እና ድንቅ የአዕዋፍ መገኛ ነው። በቅርቡ የዋሻ መስህብ የተገኘበት፣ የራፉ ውብ የዐለት ደን አቅራቢያ ያለው እና በቅርቡ በአካባቢው የሚገነባ ማረፊያ ሲጠናቀቅ ለጎብኝዎች የበለጠ ሳቢና ምቹ እንደሚሆን ጠቁመዋል።
ኢትዮጵያ በርግጥም የተትረፈረፈ ሀብት ምድር መሆኗን በማውሳት እንሰባሰብ፣ ለማለም እንድፈር፣ የጋራ ነጋችንን በጋራ እንገንባ ሲሉ ጥሪ አቅርበዋል።