የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት በሚቀጥሉት አስር ቀናት በተለያዩ አካባቢዎች ከቀላል እስከ ከባድ ዝናብ እንደሚኖር ገልጿል።
ኢንስቲትዩቱ በደቡብ ምዕራብ፣ ምዕራብ፣ ሰሜን ምዕራብ፣ ሰሜን እና መካከለኛው አካባቢዎች የዝናብ ሁኔታ እየተስፋፋ እንደሚሄድ አስታውቋል። ይህ ሁኔታ የአፈር እርጥበትን ያሻሽላል ተብሏል።
የገጸ ምድር ውሃ ፍሰት በተከዜ፣ መረብ፣ አባይ፣ ባሮ አኮቦ፣ ኦሞ፣ ጊቤ እና አዋሽ ተፋሰሶች ከመካከለኛ እስከ ከፍተኛ መጠን ይኖራል። በገናሌ ደዋ፣ ዋቤ ሸበሌ እና ኦጋዴን ተፋሰሶች ደግሞ መጠነኛ እስከ መካከለኛ ፍሰት ይታያል።
ኢንስቲትዩቱ የጎርፍ፣ የመሬት መንሸራተት እና የወንዞች ሙላት አደጋ ሊከሰት እንደሚችል አስጠንቅቋል። በተጋላጭ አካባቢዎች ቅድመ ጥንቃቄ እንዲደረግ መክሯል።