የኢትዮጵያ ጉምሩክ ኮሚሽን ከግንቦት 27 እስከ ሰኔ 3 ቀን 2018 ዓ.ም ባደረገው ክትትል ከ989 ሚሊየን ብር በላይ የሚገመቱ የኮንትሮባንድ እቃዎችን መያዝ ተችሏል።
ከዚህ ውስጥ 969 ነጥብ 4 ሚሊየን ብር የሚገመቱ የገቢ እና 20 ነጥብ 5 ሚሊየን ብር ግምት ያላቸው የወጪ የኮንትሮባንድ እቃዎች መሆናቸውን ኮሚሽኑ አስታውቋል። የኮንትሮባንድ እቃዎቹ ከፌደራልና ከክልል የፖሊስ ተቋማት እንዲሁም ከህብረተሰቡ ጋር በመሆን በተደረገው ክትትል ተይዘዋል።
በዚህ ክትትል 16 ተጠርጣሪዎችና 21 ተሽከርካሪዎች መያዛቸው ተገልጿል። የተያዙት እቃዎች አዳዲስና ልባሽ ጨርቆች፣ ኤሌክትሮኒክስ፣ የግንባታ እቃዎች፣ ቡና፣ ጥራጥሬ፣ የተሽከርካሪ መለዋወጫ፣ የመዋቢያ እቃዎች፣ ጫት፣ አደንዛዥ እጾች፣ መድኃኒት፣ ማዕድናት፣ የቁም እንስሳትና የውጭ ሀገር ገንዘቦችን ያካትታሉ።
ኮንትሮባንድ በሀገር ኢኮኖሚ የሚያሳድረውን ተጽእኖ ለመከላከል ሁሉም ባላድርሻ አካላትና ህብረተሰቡ የበኩላቸውን ሊወጡ እንደሚገባ ኮሚሽኑ አመልክቷል።