የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሺዴ ሀገራት ቀውሶችን ለመከላከል ዓለም አቀፍ የፋይናንስ ተቋማት አሰራር መሻሻል እንዳለበት ገለጹ። ይህን ያሉት በለንደን በሚካሄደው ዓለም አቀፍ የአጋርነት ጉባኤ ላይ ነው።
አቶ አሕመድ ሺዴ እንደተናገሩት ሀገራት የፋይናንስ ቀውሶችን ቀድመው ለመከላከል ዘላቂ መፍትሄ የሚያመጣ ስርዓት መፍጠር ይገባል። ዓለም በአየር ንብረት ለውጥ፣ የጂኦፖለቲካዊ ክፍፍል፣ የእዳ ጫና እና የአቅርቦት ሰንሰለት መስተጓጎል ችግሮች ውስጥ መሆኑን ጠቅሰዋል።
እነዚህ ችግሮች በተለይ በማደግ ላይ ያሉ ሀገራትን እንደሚጎዱ አመልክተዋል። ሚኒስትሩ ሀገራት በራሳቸው የኢኮኖሚ ፖሊሲ የዜጎቻቸውን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በቂ ነፃነት ሊኖራቸው እንደሚገባ አስረድተዋል።
ኢትዮጵያ ማክሮ ኢኮኖሚን ማረጋጋት፣ ዲጂታል ትራንስፎርሜሽን እና የታዳሽ ኃይል ልማትን ጨምሮ በሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያዎች ላይ ትሰራለች ብለዋል። ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ ድጋፍ ተግባራት የሀገራትን ሉዓላዊነት ማክበር እንዳለባቸውም አመልክተዋል።