የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ ታላቁ የሕዳሴ ግድብና የቢሾፍቱ አውሮፕላን ማረፊያ ኢትዮጵያን የቀጣናው ማዕከል እያደረጓት መሆኑን ተናግረዋል።
በለንደን የተካሄደው ስድስተኛው የኢትዮጵያና ዩናይትድ ኪንግደም የንግድና ኢንቨስትመንት ፎረም ላይ ሚኒስትሩ ኢትዮጵያ በኢኮኖሚ ማሻሻያዎች የውጭ ምንዛሪ ችግሮችን በዘላቂነት እየፈታች መሆኑን አመልክተዋል።
በተለይም ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ታዳሽ ኃይልን በማልማት የሀገር ፍላጎትን ከማሟላት ባለፈ ኢትዮጵያን የቀጣናው የኃይል ማዕከል እያደረጋት ነው። የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያም በአቪዬሽን፣ ሎጂስቲክስና ቱሪዝም ዘርፎች ኢንቨስትመንትና የሥራ ዕድል እየፈጠረ ነው።
በተጨማሪም 17 የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ መገጣጠሚያ ፋብሪካዎች መጀመራቸውና ቁጥራቸውን እስከ 60 ለማድረስ መታቀዱ ተገልጿል። የአይ ኤም ኤፍ ትንበያ መሠረት የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በዚህ ዓመት በ9 ነጥብ 2 በመቶ ያድጋል ተብሏል።