ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በበጀት ዓመቱ የታቀደውን 10.2 በመቶ የኢኮኖሚ ዕድገት ለማሳካት ጊዜ ማባከን እንደሌለበት አስገነዘቡ። ከእንጦጦ እስከ ቀጨኔ መድኃኔዓለም ያለውን የመልሶ ማልማትና የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክት ሥራ አስጀመሩ።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከእንጦጦ እስከ ቦሌ ያለው የሸገር ፕሮጀክት በአብዛኛው መጠናቀቁንና የቀሩት ክፍሎች በሚቀጥሉት ሁለት እና ሶስት ወራት ውስጥ ሙሉ በሙሉ ሥራ ላይ እንደሚውሉ ተናግረዋል። በእንጦጦ ተራራ ላይ የተከናወነው የኢንጆሪ ልማት ከፍተኛ ውጤት ማሳየቱንና ብርቱካን፣ ሎሚ፣ የደጋ ቡና እና ልዩ ማር እየተመረተ መሆኑን አንስተዋል።
የባሕር ዛፍን በማስወገድ በምትካቸው ሀገር በቀል ዛፎችን የመትከል ሥራ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸው ይህም የተራራውን ውሃ የመያዝ አቅም ለማሳደግ እንደሚረዳ ጠቁመዋል። በተራራማው አካባቢ አፈር እንዳይሸረሸር በኮንሶ ሙያተኞች የተገነቡት እርከኖች የገጠር እውቀትን ለከተማ ልማት የመጠቀም ትልቅ ማሳያ እንደሆነ አመልክተዋል።
ቀደም ሲል በወንዙ ዳርቻ የነበሩት የተጨናነቁ ቤቶች ለጎርፍ አደጋ የተጋለጡና ለመንገድ የማይመቹ እንደነበሩ አስታውሰው አሁን ግን አካባቢው ሙሉ በሙሉ ተቀይሮ ለሰዎች መዝናኛና እንቅስቃሴ ምቹ መሆኑን አብራርተዋል። የአዲስ አበባ ነዋሪዎችና ጎብኚዎች ጠዋት ጠዋት በዚህ የልማት መስመር ላይ በእግር በመጓዝ ጤናቸውን እንዲጠብቁና የሀገራቸውን ውበት እንዲያደንቁ ጥሪ አቅርበዋል።