ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የገጠር ኮሪደር ልማት አካል የሆነውን ዘመናዊ የሀማሳ ሞዴል መንደር በሰኔ 25 ቀን መርቀዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በአዲስ አበባ ባስተላለፉት መልዕክት በየአካባቢው የሚከወኑ የልማት ሥራዎች ኢትዮጵያን ወደምናስበው ከፍታ የመውሰድ አቅም እንዳላቸው ተናግረዋል።
የገጠር ኮሪደር ልማት ሥራ የአካባቢው አርሶ አደሮች የተሻለ ኑሮ እንዲኖሩ ያደርጋል ብለዋል። አምና መንግሥት በተለያዩ ቦታዎች ሞዴል ቤቶችን ሲገነባ ዘንድሮ በምዕራብ አባያ አርሶ አደሮች ራሳቸው ወጪ አድርገው መሥራታቸውን አመልክተዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከማሰልጠንና ድጋፍ ውጪ ወጪው ሙሉ ለሙሉ በአርሶ አደሩ እንደተሸፈነ ተናግረዋል። አርሶ አደሮች በጓሮው አትክልት፣ ፍራፍሬ፣ ማር፣ ዓሳ፣ ዶሮ እና የእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶችን በማምረት ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል።
ንጽህና እና ምግብ ካለ ጤና አለ ብለው እነዚህ ጉዳዮች ከፍተኛ ትኩረት ሊሰጣቸው እንደሚገባ አሳስበዋል። አርሶ አደሮች የጀመሩትን መልካም ጅማሮ ማጠናከር እንዳለብንም አጽንኦት ሰጥተዋል።