ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በቦረና ዞን የተገነቡ የውሃ አቅርቦትና መስኖ ፕሮጀክቶችን ጎብኝተው ለወደፊት ትውልድ ግብርና እምቅ አቅም እያዘጋጁ መሆናቸውን ተናግረዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማሕበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት በምሥራቅ ቦረናና ቦረና ዞኖች የተገነባው ግዙፍ የውሃ አቅርቦት ፕሮጀክት ንጹሕ ውሃ በማቅረብ የማሕበረሰቡን ሕይወት እየቀየረ መሆኑን አመልክተዋል።
በፊና ኦሮሚያ የመስኖ ፕሮጀክቶች አማካኝነት በጎሞሌ ወረዳ የተገነቡ 18 የመስኖ ግድቦችን የጎበኙት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከሦስት ዓመት በፊት በአካባቢው በደረሰው ድርቅ ከሦስት ሚሊየን በላይ እንሰሳት መጥፋታቸውን አስታውሰዋል።
በአንድ ግድብ ብቻ በቀን ከ150 ሺህ በላይ ከብቶች ውሃ እንደሚያገኙና ግድቦቹ ለመጠጥ ውሃና ለግብርና ስራ እንደሚውሉ ተናግረዋል። መንግሥት በአካባቢው 30 የፊና ፕሮጀክቶችን ለማጠናቀቅ ሰፋፊ ስራዎችን እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።