በአዳማ ከተማ በ6.2 ቢሊየን ብር ወጪ የተገነባው የንጹህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክት ተመርቆ ለአገልግሎት ተከፍቷል። ፕሮጀክቱ ከ1.1 ሚሊየን በላይ ነዋሪዎችን ያገለግላል።
የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር ከኦሮሚያ ክልልና አዳማ ከተማ አስተዳደር ጋር በመተባበር ፕሮጀክቱን አስገንብቷል። ፕሮጀክቱ 15 አዳዲስ የከርሰ ምድር ውሃ ምንጮችን ያካትታል።
በተጨማሪ 10 ግዙፍ የውሃ ማጠራቀሚያዎች፣ 245 የዋና ሥርጭት መስመሮች እና ባለ አምስት ወለል የአስተዳደር ቢሮ ህንጻ ተገንብተዋል። የጨፌ ኦሮሚያ አፈ ጉባዔ ሰአዳ አብዱረህማን ፕሮጀክቱ የውሃ ጥያቄዎችን በዘላቂነት ይፈታል ብለዋል።
የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴዔታ አምባሳደር አስፋው ዲንጋሞ መንግስት ተመሳሳይ ፕሮጀክቶችን በሀገሪቱ ከተሞች ሁሉ ለመገንባት እንደሚቀጥል ገልጸዋል። የኦሮሚያ ክልል ውሃና ኢነርጂ ቢሮ ሃላፊ ሚሊየን በቀለ (ዶ/ር) ፕሮጀክቱ ዘመናዊ መሳሪዎችን የተጠቀመ መሆኑን አስረድተዋል።