የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ካቢኔ የ2019 ዓ.ም ረቂቅ በጀት 502 ነጥብ 27 ቢሊየን ብር አድርጎ ወደ ምክር ቤት አመራ። በጀቱ ካለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር 43.45 በመቶ ጭማሪ አሳይቷል።
ካቢኔው በዛሬው የ5ኛ ዓመት 12ኛ መደበኛ ስብሰባ ላይ የበጀት ረቂቁን አጽድቆ ወደ ከተማው ምክር ቤት እንዲመራ ወስኗል።
ከጠቅላላው ወጪ 71 በመቶ ለድህነት ቅነሳና ለዘላቂ ልማት ግቦች ሲሆን 29 በመቶ ደግሞ ለአስተዳደራዊ ወጪዎች ተደልድሏል። ልዩ ትኩረት ለመንገድ፣ ውሃ፣ መኖሪያ ቤትና ሌሎች የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች እንዲሁም ለትምህርትና ጤና አገልግሎቶች ተሰጥቷል።
ካቢኔው በተጨማሪ የገቢ ማመንጨት አቅም ጥናት፣ የስልጠና ተቋም ደንብ፣ የማዘጋጃ ቤታዊ ክፍያ ደንብና ሀገራዊ ፋይዳ ላላቸው ፕሮጀክቶች የመሬት ምደባ ላይ ውሳኔዎችን አሳልፏል።