የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ሕዝቡ ለሚያነሳቸው ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት የቀጣይ 90 ቀናት ዕቅዳቸውን በልዩ ትኩረት እንደሚፈጽሙ አስታወቁ።
ከንቲባዋ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት የከተማ አስተዳደሩ የ90 ቀናት የመንግሥትና የፓርቲ ስራዎች ዕቅድ ላይ ተወያይተው ወደ ተግባር እንዳስገቡ ተናግረዋል።
ዋና ዋና ተግባራት መካከል የመልካም አስተዳደር ችግሮችን መፍታት፣ የኑሮ ውድነትን ማረጋጋትና የመሶብ አንድ ማዕከል ዲጂታል አገልግሎትን ማስፋት ይገኙበታል። በተጨማሪም የስራ እድል ፈጠራ፣ የሴቶችና ወጣቶች ተጠቃሚነት፣ የአረንጓዴ ዐሻራ ልማት፣ የከተማ ግብርናና የሌማት ትሩፋት፣ የሰላም ግንባታና የገቢ አሰባሰብን ማጠናከር እንዲሁም የንግድ ስርዓቱን መግራት ላይ በትኩረት እንደሚሰራ አመልክተዋል።
የኮሪደር ልማትና የወንዝ ዳርቻ ልማት ስራዎችን ጨምሮ ያልተጠናቀቁ ፕሮጀክቶችን በተያዘላቸው ጊዜና በጀት በጥራት ለማጠናቀቅ ተዘጋጅተናል ብለዋል። አዲሱ በጀት ዓመት ህዝባችንን ይበልጥ የምናገለግልበትና አዲስ አበባን የብልፅግና ተምሳሌት የማድረግ ጉዟችንን የምናረጋግጥበት እንዲሆን በጠንካራ ክትትልና ድጋፍ እንፈጽማለን ሲሉ አክለዋል።