የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ምርጫ ያሸነፈው ፓርቲ የመራጮችን ፍላጎት ለማሟላት በልማት፣ በስራ እድል እና በሰላም ላይ እንዲሰራ ጠይቀዋል።
ነዋሪዎቹ ለፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን እንደገለጹት አሸናፊው ፓርቲ የተጀመሩ ትላልቅ የልማት ፕሮጀክቶችን ማስቀጠል፣ ለወጣቶች ሰፊ የስራ እድል መፍጠር እና አስተማማኝ ሰላም ማረጋገጥ አለበት።
የከተማዋ ነዋሪ ሂሩት ጎሽሜ ሀገሪቱ በምርጫ ማግስት ላይ መገኘቷን አስታውሰው ስልጣን የሚረከበው አካል ሙሉ ትኩረቱን ለሀገርና ለዜጎች በሚጠቅሙ ስራዎች ላይ ማድረግ እንዳለበት ተናግረዋል።
ወይዘሮ ጸሐይነሽ ማሞ አዲሱ መንግሥት ሀገርን በሰላም፣ በፍቅር እና በሕብረት እንዲመራ ጠይቀዋል። የሴቶችና ህጻናት መብት እንዲጠበቅ እና እኩልነት እንዲረጋገጥ አጽንዖት ሰጥተዋል።
አቶ ብርሃኑ ከማል ደግሞ የትኛውም ፓርቲ ለስልጣን ቢመጣ ከዜጎች ጋር በቅርበት በመተባበር ሀገርን በታማኝነት ማገልገል እንዳለበት ገልጸዋል።