የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ ብልጽግና ፓርቲ ሀገርን ለማሻገር የሚያመጡ ፖሊሲዎችን እየተገበረ መሆኑን ተናግረዋል። በባሕር ዳር ከተማ የተደረገ ውይይት ላይ ይህን አስታውቀዋል።
አቶ አረጋ ከበደ ዘላቂ ሰላም ለማምጣት መንግሥት ሁሉንም የሰላም አማራጮች እየተጠቀመ መሆኑን አስታውቀዋል። ሰላማዊ እና ሕጋዊ መንገድን ተከትሎ ለሚመጣ ማንኛውም አካል የመንግሥት በር ክፍት መሆኑን አጽንኦት ሰጥተዋል።
የኃይማኖት አባቶች፣ የሀገር ሽማግሌዎች እና እናቶች ወደ ጫካ የገቡትን ኃይሎች መምከር እንዳለባቸው ገልጸዋል። የአገልግሎት አሰጣጥ ችግሮችን በዘመናዊ አሠራር ለመፍታት ጥረት እየተደረገ መሆኑንም አንስተዋል።
ባሕር ዳር ትልቅ የቱሪዝም መዳረሻ መሆኗን የገለጹት ርዕሰ መስተዳድሩ ዘርፉን ለማዘመን ደረጃቸውን የጠበቁ ሆቴሎች እንደሚያስፈልጉ ተናግረዋል። ባለሃብቶች በስፋት እንዲሰማሩ እና የተጀመሩ የልማት ሥራዎች እንዲቀጥሉ የሕዝቡ ድጋፍ እንደሚያስፈልግ አመልክተዋል።
የውይይቱ ተሳታፊዎች በከተማዋ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ሥራዎችን እና ለወጣቶች እየተፈጠረ ያለውን የሥራ እድል አመስግነዋል። ከተማዋን በማስዋብ እና ሰላምን በማረጋገጥ ከመንግሥት ጎን ሆነው እንደሚሠሩ አረጋግጠዋል።