የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ የፖሊስ ሠራዊት በሰው ኃይል ብቁና በአሰራር ዘመናዊ እንዲሆን የሚደረገውን ስራ አመሰገኑ።
ከንቲባዋ በማሕበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት የመዲናዋን የፖሊስ አመራሮችና አባላት ባካሄዱት በ100 ቀናት እቅድ የተከናወኑ የሪፎርም ስራዎች ማጠቃለያ ግምገማ ላይ በመገኘት ማበረታታቸውን ገልጸዋል።
በሪፎርም በተያዙት በመልካም አስተዳደርና አገልግሎት አሰጣጥ ዙሪያ ባለፉት 100 ቀናት ትግበራዎች የፖሊስ ሠራዊት ገለልተኛ ሆኖ በሕግና በሕዝብ የተጣለበትን አደራ በአግባቡ የሚወጣ ተቋም ሆኖ እንዲጠናከር እየተሰራ ነው።
ከተማ አስተዳደሩና ነዋሪው ሕዝብ የተቋሙንና የሠራዊቱን ስም የሚያጠለሹ ስህተቶችን በማረም ጥሩ የሚሰሩትን በማበረታታት የሚሰራውን ስራ እንደሚደግፍ አረጋግጠዋል።