የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የ2018 በጀት ዓመት የማጠቃለያ ስራዎች አፈፃፀም ግምገማ ጀመረ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ ለሦስት ቀናት በሚቆየው መድረክ ግቦች አፈጻጸም እንደሚገመገም አስታወቁ።
የተጠናቀቀው በጀት ዓመት የአምስት ዓመት ስትራቴጂክ እቅድ ማጠቃለያ መሆኑን ከንቲባዋ ገልጸዋል። የበጀት ዓመቱን አፈፃፀም ከባለፉት አምስት ዓመታት ጋር አያይዘው ይገመግማሉ።
በርካታ ስኬቶች መመዝገባቸውን ጠቁመው ከተማዋን የልማትና የሰላም ማዕከል ማድረግ መቻላቸውን አመልክተዋል። በሰው ተኮር ስራዎች ማህበራዊ ፍትህ፣ ፅዳት፣ አረንጓዴነትና ውበት መጎልበቱንም ገልጸዋል።
ተግዳሮቶችን በተመለከተ የአመራር ውጤታማነት፣ የኑሮ ውድነትና የፍልሰት ጉዳዮች በጥልቀት እንደሚታዩ አመላክተዋል። በቀጣይ የትኩረት አቅጣጫዎች ዙሪያም ውይይት ይደረጋል።