የኦሮሚያ፣ ቤኒሻንጉል ጉሙዝ እና ጋምቤላ ክልሎች በአሶሳ ከተማ የተገነባውን የጋራ ሰላምና ልማት ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት ሕንጻ በይፋ መርቀዋል። ይህ ተግባር በክልሎቹ መካከል ያለውን ትብብር የበለጠ ለማጠናከር ያለመ ነው።
በመረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሐሰን፣ የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳደር ሽመልስ አብዲሳ እና የጋምቤላ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ጋትሉዋክ ሮን ተገኝተዋል።
አቶ አሻድሊ ሐሰን ሦስቱ ክልሎች በጋራ የሚያከናውኗቸው የሰላምና ልማት ሥራዎች ትብብርን እንደሚያጠናክሩ ተናግረዋል። የሕንጻው ግንባታ ለሁለንተናዊ ብልጽግና ያተኮረ መሆኑንም አመልክተዋል።
አቶ ሽመልስ አብዲሳ በበኩላቸው የጋራ ምክር ቤት ከተቋቋመ በኋላ የተከናወኑ የመሠረተ ልማት ሥራዎች በክልሎቹ መካከል ያለውን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ትስስር እንደሚያጠናክሩ ገልጸዋል። ዶክተር ጋትሉዋክ ሮን ደግሞ ጽሕፈት ቤቱ ማኅበረሰቡን በአገልግሎት አሰጣጥ እያገለገለ መሆኑን አብራርተዋል።
የአራት ወለል ሕንጻው ግንባታ 300 ሚሊየን ብር ወጪ ተደርጓል።