የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሽመልስ አብዲሳ በክልሉ የትምህርት ተደራሽነትን ለማሳደግ በተደረጉ ጥረቶች ከፍተኛ ውጤት እንደተመዘገበ አስታውቀዋል። ይህም በቢሾፍቱ ከተማ በተከበረው የኦሮሚያ ትምህርት ቢሮ 33ኛ ዓመት የምስረታ በዓል ላይ ተነግሯል።
አቶ ሽመልስ አብዲሳ ትምህርት የበለጸገች ሀገርን ለመፍጠር የትውልድ ምንጭ እንደሆነ ገልጸዋል። በክልሉ ከባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር የትምህርት ተደራሽነትን ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን አመልክተዋል።
መምህራን በዚህ ስኬት ውስጥ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከታቸውን ገልጸው የክልሉ መንግስት የትምህርት ጥራትን ለማሻሻል ድጋፉን እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። በአሁኑ ጊዜ በኦሮሚያ 12.4 ሚሊየን ተማሪዎች በትምህርት ላይ መሆናቸውን አንስተዋል።
አፋን ኦሮሞን የቴክኖሎጂ ቋንቋ ማድረግ መቻሉን ጠቁመው ተጨማሪ ስኬቶችን ለማስመዝገብ ተጨማሪ ጥረት እንደሚያስፈልግ አፅንኦት ሰጥተዋል።