ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በያቤሎ ከተማ የተገነባውን የቦረና ባሕል ማዕከል አስመርቀዋል። ማዕከሉ የቦረናን ባህል፣ ታሪክ እና ፍልስፍና ለትውልድ የማሸጋገር ሚና ይኖረዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዛሬው ዕለት ማዕከሉን ባስመረቁበት ወቅት ቦረና የዓለም ታላቅ ሕዝብ መሆኑን ገልጸዋል። እንዲሁም ቦረና ለ300 ዓመታት በገዳ ሥርዓት ተከፋፍሎ ሲተዳደር እንደነበር አስታውሰዋል።
በመልዕክታቸው ቦረና ያለውን በማካፈል እንደሚያምን እና የዴሞክራሲ መስራች እንደሆነ ተናግረዋል። ማዕከሉ በ57.6 ሄክታር መሬት ላይ ተገንብቷል።
በአንድ ጊዜ እስከ 2,000 ሰዎች የሚያስተናግድ የስብሰባ አዳራሽ እና የቅርስ ሙዚየም ያለው ሲሆን በቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታያቸው በ2013 ዓ.ም. መሰረት ድንጋይ ተቀምጦለታል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህ ባህል በሀገሪቱ ሁሉ እንዲያድግ ጠቁመዋል።