ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የነገሌ ቦረና ገዳ አውሮፕላን ማረፊያን በይፋ መርቀዋል። የምስራቅ ቦረና ዞን ነዋሪዎች ይህ የመንግሥት ለአርብቶ አደሩ ያለውን ትኩረት ያረጋግጣል ብለዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የኢትዮጵያ አየር መንገድ 24ኛ የሀገር ውስጥ መዳረሻ የሆነውን አዲሱን የነገሌ ቦረና ገዳ አውሮፕላን ማረፊያ በዛሬው ዕለት በይፋ መርቀዋል።
የነገሌ ቦረና ከተማ ነዋሪ እንዳለ መገርሳ አውሮፕላን ማረፊያው በየብስ ትራንስፖርት ረጅም ጉዞ ምክንያት ይደርስ የነበረውን እንግልት በእጅጉ እንደሚያቃልል ተናግረዋል። ዞኑ በእንስሳት ሀብትና የስንዴ ምርት የሚታወቅ ቢሆንም ምርቱን ለማጓጓዝ የትራንስፖርት እጥረት ያጋጥም እንደነበር አስታውሰዋል።
የነገሌ ቦረና ዙሪያ ወረዳ ነዋሪ ፈንታ ገረመው አውሮፕላን ማረፊያው የዞኑን ልማትና እድገት እንደሚያፋጥንና የነገሌ ቦረና ከተማን የንግድና የቱሪዝም መዳረሻ ለማድረግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው አብራርተዋል። በዞኑ ሊበን ወረዳ ነዋሪ ቢሉ ቢርቢርሳ ደግሞ ይህ ለአካባቢው ወጣቶች ሰፊ የስራ ዕድል እንደሚፈጥር ጠቁመዋል።