ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በሐረር ከተማ በማር፣ ወተትና ዶሮ እርባታ የሚካሄዱ የሌማት ትሩፋት ሥራዎች የከተማ ነዋሪዎችን የኑሮ ዘይቤ ለመቀየርና የምርት ባህልን ለማሳደግ ትልቅ አስተዋጽዖ እንዳላቸው ገልጸዋል።
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማሕበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት በሐረር ከተማ እየተከናወኑ ያሉትን የማር፣ የወተትና የዶሮ እርባታ የሌማት ትሩፋት ሥራዎችን ተዘዋውረው ጎብኝተናል ብለዋል።
በከተማው በኢኒሼቲቩ በግለሰብና በመንግሥት ደረጃ ሼዶችን በመገንባት የማር፣ የወተት፣ የእንቁላልና የዓሳ መንደሮችን የማቋቋም ሥራ በስፋት እየተሰራ እንደሚገኝ አስረድተዋል።
እንደ ሀገር የአመጋገብ ስርዓታችንን ከመሰረቱ ለመቀየር እና በምግብ እራስን ለመቻል ትልቅ ትርጉም የሚሰጠው ይህ ተግባር ተጠናክሮ የሚቀጥል ይሆናል ሲሉ አክለዋል። የእንስሳት፣ የዶሮና ዓሳ ዝርያ ማሻሻልና መኖ ማቀነባበሪዎች ላይም ትኩረት ተሰጥቶት እየተሰራበት ይገኛል።