በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህር መኩሪያ መካሻ የሚዲያ ነጻነት ከጋዜጠኝነት ሙያ ሥነ ምግባር ጋር ተጣጥሞ መተግበር እንዳለበት ተናግረዋል።
መምህር መኩሪያ መካሻ ከፋና ፖድካስት ጋር ባደረጉት ቆይታ የሚዲያ ነጻነት እና የጋዜጠኝነት ሥነ ምግባር የማይነጣጠሉ መሆናቸውን አመልክተዋል።
የጋዜጠኝነት ትምህርት ቤቶች ንድፈ ሀሳብን ከተግባር ጋር በማዋሃድ በሙያዊ ክህሎት የታነፀ የሰው ኃይል ማፍራት እንዳለባቸው ገልጸዋል። ለዚህም የተሟሉ ስቱዲዮዎችን እና የሥራ ግብዓቶችን ማመቻቸት አስፈላጊ መሆኑን አንስተዋል።
መምህሩ ሚዲያው የሀገርን ሉዓላዊነት፣ የሕዝብን አንድነት እና ብሔራዊ ጥቅምን ማስጠበቅ እንዳለበት አጽንኦት ሰጥተዋል። ኢትዮጵያውያን የሚያስማሙ እሴቶች ይበልጣሉ በማለት ሚዲያዎች አንድነትን የሚያጎሉ ትርክቶችን ላይ ትኩረት እንዲያደርጉ መክረዋል።