የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ባለፉት ዘጠኝ ወራት ውስጥ ከዘጠኝ ሺህ ኪሎ ሜትር በላይ አዳዲስ የዲስትሪቢዩሽን መስመሮችን አስፋፍቷል።
አዲስ አበባ፣ ሚያዚያ 29፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ)። በዚህ ጊዜ ውስጥ 3 ሺህ 518 ኪሎ ሜትር የመካከለኛ መስመር እና 6 ሺህ 69 ኪሎ ሜትር የዝቅተኛ መስመር ዝርጋታ ተከናውኗል። በተጨማሪም 3 ሺህ 683 አዲስ የዲስትሪቢዩሽን ትራንስፎርመሮች ተተክለዋል።
አገልግሎቱ ነባሩን መሰረተ ልማት ለማሻሻል 62 ሺህ 274 ኪሎ ሜትር የመካከለኛ መስመር እና 67 ሺህ 131 ትራንስፎርመሮች ላይ የቅድመ መከላከል ምርመራ አካሂዷል። በዲስትሪቢዩሽን ኔትወርክ ላይ ከተገኙ ለኃይል መቆራረጥ መንስኤዎች 92 በመቶ እና በትራንስፎርመሮች ላይ 86 በመቶ የማስተካከያ ርምጃዎች ተወስደዋል።
በተጨማሪ 3 ሺህ 99 ኪሎ ሜትር የመካከለኛና ዝቅተኛ መስመር መልሶ ግንባታ ተከናውኗል። በ1 ሺህ 579 ነባር ትራንስፎርመሮች ላይም የአቅም ማሻሻያ ተደርጓል።