የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት በመጪው ክረምት የኃይል መቆራረጥን ለመቀነስ ዝግጅት እያደረገ መሆኑን አስታወቀ። በአዲስ አበባ እና በሀገር አቀፍ ደረጃ የመስመር ፍተሻና ጥገና ሥራዎች ተከናውነዋል።
የአገልግሎቱ የኤሌክትሪክ መሠረተ ልማት ሥራ አስፈፃሚ ገበየሁ ሊካሳ (ዶ/ር) የተደረጉ ጥናቶች የኃይል መቆራረጥ መንስኤዎችን እንደለዩ ተናግረዋል። ያረጁ መስመሮችን መተካትና አቅም ማሳደግ በከፍተኛ ወጪ እየተከናወነ ነው።
በአዲስ አበባ 1 ሺህ 750 ኪሎ ሜትር እና በሀገር አቀፍ ደረጃ 62 ሺህ 274 ኪሎ ሜትር የመካከለኛ መስመር ፍተሻ ተደርጓል። 67 ሺህ 131 ትራንስፎርመሮች ላይ ምርመራ ተደርጓል። በዚህም 92 በመቶው የዲስትሪቢዩሽን ኔትወርክ ችግሮችና 86 በመቶው የትራንስፎርመር ችግሮች ተስተካክለዋል።
ባለፉት ዘጠኝ ወራት 3 ሺህ 99 ኪሎ ሜትር የመካከለኛና ዝቅተኛ መስመር መልሶ ግንባታ ተከናውኗል። የሀረር፣ ወላይታ፣ ሻሸመኔ፣ ደብረ ማርቆስ፣ ጎንደርና ኮምቦልቻ ፕሮጀክቶች ተጠናቀዋል። በአዲስ አበባ የወርሃዊ የኃይል መቆራረጥ ድግግሞሽ ከ27 ወደ 15 ቀንሷል።