የኢትዮጵያ አየር ኃይል ዋና አዛዥ ሌተናል ጄኔራል ይልማ መርዳሳ የአየር ኃይሉ የሀገር ሉዓላዊነትን የማያስደፍር የሰማይ ላይ ጋሻ መሆኑን ተናግረዋል።
አዲስ አበባ ሰኔ 9 2018 ሌተናል ጄኔራል ይልማ መርዳሳ ዘመናዊ ቴክኖሎጂ የታጠቀ የማይበገር አየር ኃይል መገንባቱን አረጋግጠዋል። ይህ ኃይል ሀገርን ከባዕድ ወረራና ከባንዳዎች ሴራ ይከላከላል ብለዋል።
የውጊያ ዝግጁነት ቀዳሚ ዓላማ ውጊያን ከሩቅ ማስቀረት መሆኑን ገልጸዋል። ጠላት ወደ ውጊያ ከገባ ግን የጠላትን ህልውና እስከወዲያኛው የሚያከስም መቺ ኃይል መሆኑን አረጋግጠዋል።
በቴክኖሎጂ ሽግግርና በዘመናዊ አቪዬሽን ቴክኖሎጂዎች የተደገፈ ቋሚ ተቋም ግንባታ በቀጣናው የማይበገር ኃይል አድርጎታል ብለዋል። ጀግኖች አብራሪዎችና ቴክኒሺያኖች ሰማያትን በንቃት እየጠበቁ እንደሆነም አክለዋል።