የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ፈረንሳይ ሊዮን የመንገደኞች በረራ አገልግሎት ማስጀመሩን አስታውቋል። ይህ በፈረንሳይ ሦስተኛው መዳረሻው ሲሆን አጠቃላይ ዓለም አቀፍ መዳረሻዎቹን ወደ 146 አድርሷል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ሥራ አስፈጻሚ መስፍን ጣሰው በረራው መጀመር አፍሪካን ከዓለም ጋር የማገናኘት ጉዞ ላይ ተጨማሪ ስኬት እንደሆነ ተናግረዋል። በረራው ለተጓዦች ተጨማሪ ዕድል የሚፈጥር ሲሆን የአገራትን ትስስር ያጠናክራል ብለዋል።
በኢትዮጵያ የፈረንሳይ አምባሳደር አሌክሲ ላሜክ በረራው የሊዮንን ኢኮኖሚያዊ ግንኙነት ያጠናክራል ብለዋል። ኢትዮጵያና ፈረንሳይ በአቪየሽን ኢንዱስትሪ ዓመታት ያስቆጠረ ግንኙነት አላቸው።
አየር መንገዱ ዘመናዊ አውሮፕላኖችን በማስፋፋት የመዳረሻ ቁጥሩን ለመጨመር እየሰራ መሆኑን አስታውቋል።