በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ኤርቪን ማሲንጋ የኢትዮጵያን የኢንቨስትመንት ምሕዳር ለማስፋት የምትወስደውን እርምጃ አድንቀዋል። ይህም በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር ዶክተር ዘለቀ ተመስገን ጋር ባደረጉት ውይይት ተገልጿል።
አዲስ አበባ ውስጥ በተደረገው ውይይት ኮሚሽነሩ በኢትዮጵያ ስላሉ የኢንቨስትመንት ዕድሎች እና ኢንቨስትመንትን ለመሳብ ስለሚደረጉ ሥራዎች ገለጻ አድርገዋል። ባለሃብቶች የሚያጋጥሟቸውን ተግዳሮቶች ለመፍታት የሚደረጉ የፖሊሲ ማሻሻያዎችንም አብራርተዋል።
አምባሳደር ማሲንጋ የሪፎርም ሥራዎችን አድንቀው ማሻሻያዎቹ በተጠናከረ መልኩ ከቀጠሉ የአሜሪካ ኩባንያዎች በኢትዮጵያ ያለ ምንም ስጋት ኢንቨስት ለማድረግ ምቹ ሁኔታ እንደሚፈጠር ጠቁመዋል።
ኮሚሽነሩ በኢትዮጵያና በአሜሪካ መካከል ያለው የኢንቨስትመንት ግንኙነት ይበልጥ እንዲጠናከር ዝግጁ መሆናቸውን ተናግረዋል። የአሜሪካ ባለሃብቶች በዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ፣ በማዕድን፣ በጤና፣ በመሠረተ ልማትና በቴክኖሎጂ ዘርፎች ላይ ፍላጎት እንዳላቸው ተገልጿል።