የኢትዮጵያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ግብፅ የቀጣናው ሀገራት ልማት እንዳይሳካ ለዘመናት ትንኮሳ ስትፈጽም እንደቆየች ገለጸ። ቃል አቀባዩ አምባሳደር ነቢያት ጌታቸው ይህን በተመለከተ መግለጫ ሰጥተዋል።
አዲስ አበባ ላይ በተደረገው መግለጫ ሚኒስቴሩ ግብፅ የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅሞች ለማዳከም ጫና እያደረገች መሆኑን አስታውቋል። በተለይም ኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ ካቀረበች በኋላ ግብፅ ይህንን ለማፈን ተጨማሪ ጫናዎችን እያደረገች ነው ተብሏል።
የኢትዮጵያ መንግስት የባህር በር ጉዳይ በሰላማዊ መንገድ መፈታት እንዳለበት እምነቱን አጽንቷል። ቃል አቀባዩ ጥያቄው በተለያዩ መንግስታትና ተቋማት ዘንድ ተቀባይነት እያገኘ መምጣቱን ገልጸዋል።