የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግስት ሃሚድ ኢትዮጵያ የሳይበር ደህንነትን ለሀገራዊ ልማትና ብሔራዊ ደህንነት ቁልፍ ስትራቴጂ አድርጋ እየሰራች መሆኑን አስታወቁ።
ወ/ሮ ትዕግስት ሃሚድ ይህን የተናገሩት 3ኛው ዓለም አቀፍ የሳይበር ደህንነት እና ሰውሰራሽ አስተውሎት ጉባዔ በአዲስ አበባ በጀመረበት ወቅት ነው።
ዳይሬክተሯ የሳይበር ደህንነት ከቴክኒክ ስራ ወደ ዓለም አቀፍ ስትራቴጂካዊ ቅድሚያ መሸጋገሩን አመልክተዋል። ደህንነቱ የተጠበቀ ዲጂታል ምሕዳር የሀገር ሉዓላዊነት መሠረታዊ ምሰሶ መሆኑንም አጽንእተዋል።
ኢትዮጵያ በ2004 ዓ.ም ያወጣችውን የመጀመሪያውን ብሔራዊ የሳይበር ደህንነት ፖሊሲ በ2017 ዓ.ም አሻሽላለች። ቁልፍ መረጃ መሠረተ ልማት ጥበቃ፣ የግል መረጃ ጥበቃ፣ የኤሌክትሮኒክስ ግብይት እና የሳይበር ወንጀል ጥበቃ አዋጆችን ጨምሮ ህጋዊ ማዕቀፎች መዘጋጀታቸውንም ጠቁመዋል።