የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ እና ኢጋድ በቀጣናዊ የፀጥታ ትብብር ላይ ስትራቴጂያዊ ስምምነት ተፈራርመዋል።
አዲስ አበባ ሐምሌ 2 2018 የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ጠቅላይ አዛዥ ኮሚሽነር ጄነራል ደመላሽ ገ/ሚካኤል እና የኢጋድ ዋና ጸሐፊ ወርቅነህ ገበየሁ ዶ/ር ስምምነቱን ተፈራርመዋል።
ስምምነቱ የኢትዮጵያ ፖሊስ ዩኒቨርሲቲን በመጠቀም የህግ አስከባሪዎችን በስልጠና በምርምርና በጋራ ጥናቶች ለማበልጸግ ያለመ ነው። ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ ገ/ሚካኤል ስምምነቱ የኢትዮጵያ ፖሊስ በሪፎርም ያገኘውን አቅምና ተሞክሮ ለኢጋድ አባል ሀገራት ለማካፈል የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል።
የኢጋድ ዋና ጸሐፊ ወርቅነህ ገበየሁ ዶ/ር የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ እያሳየ ያለውን ትልቅ ለውጥና ዕድገት አመስግነዋል። የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ታምራት ሙሉጌታ ዶ/ር ስምምነቱ የቀጣናውን የጸጥታ ኃይል ለማብቃት የጋራ ስልጠናዎችን ለመስጠትና የመረጃ ልውውጥን ለማዘመን ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ገልጸዋል።