በአማራ ክልል የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ 158 መካከለኛና ከፍተኛ አምራች ኢንዱስትሪዎች ምርት ማምረት ጀምረዋል። የክልሉ ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ቢሮ እንደገለጸው እነዚህ ኢንዱስትሪዎች በአዲስ መልክ ምርት ማምረት ጀምረዋል።
የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ክልላዊ የማጠቃለያ መርሐ ግብር በኮምቦልቻ ከተማ እየተካሄደ ነው። በዚህ መርሐ ግብር ላይ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ፣ የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል እና ሌሎች የፌዴራልና የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች ተገኝተዋል።
የቢሮ ምክትል ኃላፊ ተፈሪ ታረቀኝ እንዳሉት ንቅናቄው በአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፉ የነበሩ ችግሮችን እየፈታ መጥቷል። ባለሃብቶች ያነሷቸው ጥያቄዎች ደረጃ በደረጃ መፍታት እንደተቻለ ገልጸዋል።
በተያዘው በጀት ዓመት ባለፉት ወራት ብቻ 158 ኢንዱስትሪዎች በአዲስ መልክ ማምረት መጀመራቸውን ቢሮው አመልክቷል። በመርሐ ግብሩ ላይ 145 ኢንዱስትሪዎች ምርትና አገልግሎታቸውን እያስተዋወቁ ነው። መሪ ሃሳቡም “ኢትዮጵያ ታምርት ለሁለንተናዊ ሉዓላዊነት” ነው።