የኦጋዴን ብሔራዊ ነጻነት ግንባር ምክትል ሊቀመንበር አሕመድ ያሲን በሶማሌ ክልል የተመዘገቡ የልማት ስኬቶች እንዲጠናከሩ የበኩሉን ድርሻ ለመወጣት ዝግጁ መሆናቸውን ተናገሩ።
አዲስ አበባ፣ ሰኔ 4፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ)። አሕመድ ያሲን ከለውጡ በፊት በነበረው አግላይ የፖለቲካ ሥርዓት ምክንያት ኦብነግ የጫካ ትግል ውስጥ እንደነበር አስታውሰዋል። በአገሪቱ የመጣው ለውጥ ተከትሎ በተፈጠረው ምቹ የፖለቲካ ምህዳር የትጥቅ ትግሉን በመተው ሰላማዊ የፖለቲካ ትግል ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል።
የሃሳብና የፖሊሲ ልዩነቶች እንደተጠበቁ መሆናቸውን አንስተው በሀገር ሉዓላዊነት፣ በብሄራዊ ጥቅምና በዜጎች ሰላምና ደህንነት ጉዳይ ላይ የተለየ አቋም እንደሌላቸው አስረድተዋል። በሶማሌ ክልል ለመጣው ዘላቂ ሰላምና የሚታዩ የልማት ስራዎች ፓርቲያቸው አድናቆት እንዳለው ገልጸዋል።
ኦብነግ በ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ በመሳተፍ በክልሉ ያለውን ጠንካራ የፖለቲካ ተሳትፎ ማሳየቱን ተናግረዋል። በፓርቲው ስም ከታጠቁ ኃይሎች ጋር ጥምረት በመፍጠር የባዕድ ተልእኮ ለጥፋት የሚንቀሳቀሱ ባንዳዎች መኖራቸውን አንስተው በኦብነግ ውስጥ ምንም ስፍራ እንደሌላቸው ተናግረዋል።