በጋምቤላ ክልል የእርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ እንደገለጸው አርሶ አደሮች በአቮካዶ፣ ሙዝ፣ ፓፓያ እና ብርቱካን ልማት በማተኮር የቤተሰብ ገቢያቸውን እያሳደጉ ነው።
የቢሮው ኃላፊ አቶ አንድሪው ቱት በተለያዩ አካባቢዎች የአትክልትና ፍራፍሬ ልማትን በማስፋፋት የአርሶ አደሮችን ተጠቃሚነት ለማሻሻል በትኩረት እየተሠራ መሆኑን ተናግረዋል።
አርሶ አደሮቹ ለገበያ ተፈላጊ ምርቶችን በማቅረብ የቤተሰብ ገቢያቸውን እያሳደጉ ናቸው። ይህም በአካባቢው የተመጣጠነ ምግብ ተደራሽነትን በማሻሻል የምግብ ዋስትና ግብን ለማሳካት አስተዋፅኦ እያደረገ ነው።
የተገኘውን ውጤት ለማስቀጠል የተለያዩ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም ከፍተኛ ምርትና ጥራት ያላቸው የአቮካዶ ችግኞች እየተሰራጩ ናቸው። በዘንድሮው ክረምት ከአረንጓዴ ዐሻራ ልማቱ ጋር በማቀናጀት ከ8 ሚሊየን በላይ የፍራፍሬና ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት እየተደረገ ነው።