የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ የበጎ ፈቃድና የልማት ሥራዎችን በጥብቅ ቅንጅት መምራት እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
ከንቲባዋ የክረምት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት፣ የአረንጓዴ ዐሻራ፣ የቤት ግንባታና የማህበራዊ ድጋፍ ሥራዎችን አፈጻጸም ከከተማዋ አመራሮች ጋር ገምግመዋል። በክፍለ ከተሞችና በተቋማት መካከል የአፈጻጸም ልዩነቶች በመኖራቸው ቀጣይ ሥራዎች በጥብቅ ቅንጅት ሊመሩ እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
የቤት ግንባታን ማፋጠን፣ የፍሳሽ ማለፊያ ዲችዎችን ማጽዳትና አዳዲስ ግንባታዎችን ማካሄድ እንዲሁም ከፍተኛ ሃብት ወጥቶባቸው የለመሩ ሥፍራዎችን አሰራርና ጽዳት በአግባቡ መጠበቅ ላይ በቅንጅት መስራት እንደሚገባ አመልክተዋል። በግንባታ ምክንያት በሚወጡ ተረፈ ምርቶች መንገዶችን የሚያበላሹ እና ዲችዎችን የሚዘጉ አካላት ችግሩን በአፋጣኝ እንዲያርሙና ተጠያቂ እንዲሆኑ የማድረግ ሥራ እንደሚሰራ ተናግረዋል።
የችግኝ ተከላ ከዕቅድ በላይ እንዲከናወንና ለአስፈላጊው ጥራት ትኩረት እንዲሰጥ እንዲሁም የበጎ ፈቃድ አገልግሎትንና የከተማ ጽዳትን የሕብረተሰቡ ባሕል የማድረግ ሥራ በትኩረት እንደሚከናወን ጠቁመዋል። የተማሪዎችን ውጤታማነት ለማረጋገጥ የሚሰጠው የክረምት ማጠናከሪያ ትምህርትና የጎልማሶች ትምህርት በልዩ ትኩረት እንደሚመሩም አስፍረዋል።