አዲስ አበባ፣ ግንቦት 11፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) በኢትዮጵያ የስታቲስቲክስ ዘርፍ ልማት የግብርና ቆጠራን፣ የስነ-ሕዝብና ጤና ጥናትን ዘመናዊ ለማድረግ ያስቻለ ተጨባጭ ውጤት ተመዝግቧል አለ የፕላንና ልማት ሚኒስቴር።
በኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት የኢኮኖሚ ስታቲስቲክስ ዘርፍ ኃላፊ አብዱልአዚዝ ሸፋ እንዳሉት የስታቲስቲክስ ልማት ፕሮግራም ዋና አላማ መንግስት ለሚያከናውናቸው ተግባራት አስፈላጊ መረጃዎችን ማምረት ነው።
በቤተሰብ፣ በድርጅትና በወርሃዊ ደረጃ የሚከናወኑ ጥናቶች መኖራቸውን የጠቀሱት ኃላፊው በየወሩ የሚከናወነው የሸማቾች ዋጋ ጥናት የኢኮኖሚ ሁኔታ የሚለይበት መሆኑን ገልጸዋል። ጥናቱ እስከ 95 በመቶ የማረጋገጫ ሁኔታንና የተለያዩ ሳይንሳዊ ዘዴዎችን በመጠቀም ይከናወናል።
በተቋሙ በየሦስት ወር የሚጠና የስራ ስምሪት ሁኔታ፣ ዓመታዊ የግብርና ናሙና ጥናት እንዲሁም በየአምስት አመት የሚከናወኑ የስነ ሕዝብ እና ጤና ጥናቶች መኖራቸውን ገልጸዋል። በኢትዮጵያ የሰብል፣ የቤት እንስሳት፣ የአካባቢ እንዲሁም የከተማና የገጠር ስታቲስቲክስ መኖራቸውን ያነሱት ኃላፊው ባለፉት ዓመታት በጤና እና ግብርና ስራዎች ከፍተኛ ውጤት መገኘቱን በተደረገው ጥናት መረጋገጡንም አንስተዋል።